ከተመዘኑት ሆቴሎች ውስጥ 45 በመቶ የሚሆኑት የደረጃ ምደባ መመዘኛን ማለፍ አልቻሉም
December 21, 2017 - በሀገር አቀፍ ደረጃ የተካሄደውን የሆቴሎች ደረጃ መመዘኛ ተከትሎ በርካታ ሆቴሎች የብቃት መመዘኛ ደረጃዎችን ማለፍ አልቻሉም፡፡ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ማክሰኞ ታህሳስ 10 ቀን 2010 ዓም በሆቴሎች ደረጃ ምደባ ዙሪያ ከባለድርሻ አካለት ጋር ባደረገው ውይይት እንደተመለከተው አዲስ አበባን ጨምሮ በበርካታ ክልሎች ያሉ 365 ሆቴሎች ተመዝነው ተገቢውን ደረጃ ማሟላት የቻሉት 198 ብቻ ናቸው፡፡ ቀሪዎቹ 167 የብቃት ማረጋገጫውን ማለፍ ባለመቻላቸው ውጤታቸው ሊገለፅ ያልቻለ መሆኑ ተመልክቷል፡፡
በዚሁ ዙሪያ ሰፋ ያለ የጥናት ፅሁፍ ያቀረቡት በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቱሪስት አገልግሎት የብቃት ማረጋገጥና ደረጃ ምደባ ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ ደርበው፤ የሆቴሎች የደረጃ ምደባ በሀገር አቀፍ ደረጃ 365 ሆቴሎች የተመዘኑ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በአዲስ አበባና በክልሎች ደረጃውን አሟልተው ከአንድ እስከ አምስት ያለውን የሆቴል ኮከብ ደረጃ መውሰድ የቻሉት 198 ብቻ ናቸው፡፡
በዚህም በአዲስ አበባ ከተመዘኑት 139 ሆቴሎች ውስጥ ደረጃውን አሟልተው ከአንድ እስከ አምስት ያለውን የኮከብነት ደረጃ ማግኘት የቻሉት 80ዎቹ ብቻ መሆናቸውን አቶ ቴዎድሮስ ጨምረው አመልክተዋል፡፡ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በኦሮሚያ ክልል ከሰባ አምስቱ ሰላሳ ሁለቱ፣ በአማራ ክልል ከስልሳው አስራ ዘጠኙ፣ በደቡብ ክልል ከአርባ አንዱ ሃያው፣ በትግራይ ክልል ከሰላሳ አንዱ አስራ አንዱ በድሬዳዋ ከአስራ ስድስቱ አራቱ እንደዚሁም በሀረር ከሶስቱ አንዱ ብቻ የብቃት ማረጋገጫውን ምዘና አልፈው የሆቴሎች የኮከብ ደረጃውን ያገኙ መሆናቸው ታውቋል፡፡
ከዚህ ቀደም የሆቴሎች የብቃት ማረጋገጫ ደረጃ ምዘና የተካሄደው የተከናወነው በፕሮጀክት ደረጃ መሆኑን ያመለከቱት ኃላፊው፤ በጊዜው በዘርፉ በቂ ባለሙያ ስላልነበር የውጭ ባለሙያዎች መቅጠር ግድ ሆኖ አንደነበር ገልፀዋል፡፡ ይህም በመሆኑ በ2007 ዓ.ም በተካሄደው የሆቴሎች የብቃት ማረጋገጫ ደረጃ ምደባ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዓለም የቱሪዝም ድርጅት ሥራውን በኃላፊነት ያከናወነ መሆኑ ተመልክቷል፡፡
ምዘናው የተካሄደባቸው ሆቴሎች በአዲስ አበባ፣ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በትግራይ እና በደቡብ ክልሎች እንደዚሁም በሐረሬ ክልል የሚገኙ ሲሆኑ በቀጣይም እንደ አፋር፣ኢትዮጵያ ሶማሌ እና በሌሎች ታዳጊ ክልሎች ባሉ ሆቴሎች የደረጃ ምደባው የሚካሄድ መሆኑን አቶ ቴዎድሮስ ጨምረው አመልክተዋል፡፡
ሌላው በዚሁ የምክክር መድረክ ላይ ከተነሱት አንኳር ጉዳዮች መካከል አንዱ የአዲስ አበባ ሆቴሎች ለውጭ እንግዶች ሳይቀር ዋጋቸው ውድ መሆን ሲሆን ይሄንንም ጉዳይ በተመለከተ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ መዓዛ ገብረመድህን ማሳሳቢያ ጭምር ሰጥተውበታል፡፡ ሚኒስትር ዴኤታዋ የሆቴሎቹን ዋጋ ውድነት በተመለከተ በአፍሪካ ህብረት ጭምር ቅሬታ እየቀረበ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በሆቴሎቹ ምዘና ሂደት የንፅህና ጉዳይ አሳሳቢ ሆኖ የታየ መሆኑንም ይሄው ጥናታዊ ሪፖርት ይተነትናል፡፡ በፍተሻ ከተረጋገጠው የምግብ ማዘጋጃ ቦታም ሲታይ አንድ ሶስተኛ የሚሆኑት ለመዘጋት የሚያስችል ከፍተኛ የንፅህና ጉድለት ታይቶባቸዋል ተብሏል፡፡
ምንጭ:- ሰንደቅ ጋዜጣ